Thursday, June 13, 2013

“… ካላበዱ በቀር …” - ኃይለማርያም ደሣለኝ ስለግብፅ መሪዎች

የኅዳሴ ግድብ ሥፍራየኅዳሴ ግድብ ሥፍራ

“… ካላበዱ በቀር …” - ኃይለማርያም ደሣለኝ ስለግብፅ መሪዎች

ከዕለት ወደ ዕለት በኢትዮጵያና በግብፅ መካከል የዲፕሎማሲ መካረርን እያስከተለ በመጣው በግዙፉ የኅዳሴ ግድብ ግንባታ ጉዳይ ላይ ለመነጋገር የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሞሐመድ ካመል አምር የፊታችን ዕሁድ አዲስ አበባ እንደሚገቡ ተነገረ፡፡

ኢትዮጵያና ግብፅ በአፍሪካዊነት መንፈስ ወደ ንግግር እንዲገቡ የአፍሪካ ሕብረት ሊቀመንበር ዶ/ር ንኮሣዛና ድላሚኒ ዙማ አሳሰቡ፡፡

ኅዳሴ ግድብ በግንባታ ላይኅዳሴ ግድብ በግንባታ ላይ
ግብፅ የውኃ ጥቅሜን ይጎዳል የምትለው በአፍሪካ ግዙፉ የኃይድሮ ኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ይሆናል የተባለው ኅዳሴ ግድብ ግንባታ በምንም ሁኔታ እንደማይቆም የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ትናንት ባወጣው መግለጫ አመልክቶ እንደነበር ይታወሣል፡፡

ሞሐመድ ሞርሲ - የግብፅ ፕሬዚዳንትሞሐመድ ሞርሲ - የግብፅ ፕሬዚዳንት
“ግብፅ ጦርነት አትፈልግም፤ ነገር ግን ሁሉም አማራጮች ጠረጴዛ ላይ ናቸው” ሲሉ የግብፅ ፕሬዚዳንት ሞሐመድ ሞርሲ ከትናንት በስተያ ከተናገሩ ወዲህ በሁለቱ ሃገሮች መካከል ያሉት ሁኔታዎች የተካረሩ እንደሚመስሉ ዘገባዎቹ እየጠቆሙ ነው፡፡

በቻይና ለሚያደርጉት ጉብኝት ዛሬ ከአዲስ አበባ የተነሡት የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር በጉዟቸው ወቅት አብሯቸው ለሚገኝ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ጋዜጠኛ በሰጡት ለግብፁ ፕሬዚዳንት ሃሣብ መልስ የሚሰጡ ሃሣብ ሲናገሩ “ሁሉም አማራጮች ጠረጴዛ ላይ ናቸው ሲሉ ጦርነትንም ያካትታል ማለታቸው ነው፡፡ ካላበዱ በስተቀር ይህንን አማራጭ ይወስዳሉ ብለን አናምንም፡፡” ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሣለኝም ይህንኑ የኅዳሴ ግድብ ግንባታና በዙሪያውም የተነሣውን የኢትዮ-ግብፅ ውዝግብ አስመልክቶ ዛሬ ተናግረዋል፡፡

የግብፁን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የመጭው ዕሁድ የአዲስ አበባ ጉዞ አስመልክቶ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሣደር ዲና ሙፍቲ በሰጡት መግለጫ “እኛ ሁል ጊዜ በመነጋገር እንደምናምን ስንገልፅ ቆይተናል፤ ይህ ጉብኝትም እኛ የምንፈልገው ነው” ብለዋል፡፡ “ይሁን እንጂ - አሉ ዲና ሙፍቲ ጠንከር ባሉ ቃላት አክለው - የግድቡን ሥራ የማዘግየት ወይም የማቆም አንዳችም ሃሣብ አናስተናግድም፡፡”

ን'ኮሣዛና ድላሚኒ-ዙማ - የአፍሪካ ሕብረት ሊቀመንበር፡፡ን'ኮሣዛና ድላሚኒ-ዙማ - የአፍሪካ ሕብረት ሊቀመንበር፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ኢትዮጵያና ግብፅ ውዝግቡን ለመፍታት ወደ ንግግር እንዲገቡ የአፍሪካ ሕብረት ጠይቋል፡፡

የሕብረቱ ሊቀመንበር ንኮሣዛና ድላሚኒ ዙማ ዛሬ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ “በአዲስ አስተሳሰብ ስሜትና መንፈስ ሁሉም ወገኖች አሸናፊ የሚሆኑበትን ግልፅ ንግግር መጀመር አስፈላጊ ነው፡፡ በቅኝ አገዛዝ ኃይሎች ግንዛቤና አካሄድ ሣይሆን በመላ-አፍሪካዊነትና በአፍሪካ ኅዳሴ ስሜትና መንፈስ ነው ንግግሮቹ መካሄድ ያለባቸው” ብለዋል፡፡

የቀድሞ የግብፅ አስተዳደሮች የአባይን ውኃ ሊነካ የሚችል ማንኛውንም ግድብ በወታደራዊ ኃይል የመምታት የመጠባበቂያ ዕቅድ ይዘው መኖራቸው ይታወቃል፡

No comments:

Post a Comment